ዜና ፌ.ቤ.ኮ
የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በቦረና እና አካባቢው በድርቅ ለተጎዱ የማህበረሰብ አካላት መልሶ ማቋቋሚያ የሚውል የ10 ሚሊየን ብር ድጋፍ አደረገ

የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በቦረና እና አካባቢው በድርቅ ለተጎዱ የማህበረሰብ አካላት መልሶ ማቋቋሚያ የሚውለውን የ10 ሚሊየን ብር ድጋፍ፣ ክቡር አቶ ረሻድ ከማል ለኦሮሚያ ቡሳ ጎኖፋ ሥራ አስኪያጅ ለአቶ ሀብታሙ ሲሳይ በዛሬው እለት አስረክበዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክቡር አቶ ረሻድ ከማል በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ከዚህ በፊትም ቦረናና አካባቢው ባጋጠመው ድርቅ ምክንያት ለተጎዱ የማሕበረሰብ አከላት ድጋፍ ማድረጉን አስታውሰው ፣ ኮርፖሬሽኑ በመላ አገሪቱ በሚያጋጥሙ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ችግሮች የተነሳ ለሚቀርቡ አገራዊ ጥሪዎች ባለው አቅም ሁሉ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የኮርፖሬሽኑ ማኔጅምንትም ለቦረናና አካባቢው በድርቅ ሳቢያ ተጎጂ ለሆኑ የማህበረሰብ አካላት መልሶ ለማቋቋም በአገር ዓቀፍ ደረጃ እየተደረገ ያለውን ሰብአዊ እቅስቃሴ ለመደገፍ የ10 ሚሊዮን ብር ድጋፍ እንዲደረግ ውሳኔ ላይ ደርሷል ሲሉም ተናግረዋል ዋና ሥራ አስፈጻሚው፡፡
እንደዚህ ያሉ ወቅቶችንና ችግሮችን በጋራ በመተባበርና እና በመተሳሰብ ልንሻገራቸው ስለሚገባ ኮርፖሬሽኑ በቀጣይም ለመሰል አገራዊ የድጋፍ ጥሪዎች ድጋፍ ማድረጉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ክቡር አቶ ረሻድ ከማል ባደረጉት ንግግር አረጋግጠዋል፡፡
የኦሮሚያ ቡሳ ጎኖፋ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሀብታሙ ሲሳይ በበኩላቸው ድጋፉ ክልሉ በቦረና አካባቢውን በድርቁ ሳቢያ ጉዳት የደረሰባቸውን የማህበረሰብ አከላት መልሶ ለመቋቋም የሚደረገውን የአጭር ጊዜ እቅድ እንዲሳካ የሚያግዝ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ኮርፖሬሽኑ ከበርካታ የልማት ሥራዎች ጎን ለጎን ማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት ታሳቢ በማድረግ የ10 ሚሊየን ብር ድጋፍ በማድረጉ በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልል መንግስት ስም ምስጋና አቅረባለሁም ብለዋል የቡሳ ጎኖፋ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሀብታሙ ሲሳይ ፡፡
በቦረናና አካባቢው የደረሰው ድርቅ የካፋ መሆኑን ጠቁመው እንደ ፌዴራል ቤቶች ኮርሬሽን ዓይነት ድጋፍና አብሮነት በእጅጉ እንደሚያስፈልግም አቶ ሀብታሙ ሲሳይ አስገንዝበዋል፡፡